ባሌን ያገባሁት ብርሃነን ስለሚመስል ነው ። ጥንካሬው እና ታማኝነቱ የአባቴ የብርሃነን አይነት ነው ።
መውደዳችን ውስጥ አስተዳደጋችን ተፅፏል።
አባቴ በጊዜ ነው የሚገባው ፣ እናቴን የሚወዳት መጠን ፣ የሚያከብራት አከባበር የተለየ ነው ፤ አለሙን ያገባሁት ቁርጥ ብርሃነን ስለሆነ ይመስለኛል ።
የሆነ ቀን...የሆነ ገፊ እና ቀፋፊ ቀን....አለሙ መሸርሞጡን ደረስኩበት ።
እንዴት እንደጠላሁት ። ጥላቻዬ የጀመረው መልከስከሱን ስደርስበት ነው ። ፍቅሬ እሱ ላይ ካለኝ እምነት ጋር የተዋሃደ ነበር። እምነቴ ሲተን ፣ ፍቅሬ ብቻውን መፅናት ሳይችል ቀረ ፤ አለሙን ጠላሁት ።
"ተፋተናል" የሚል ቁራጭ ወረቀት ትቼለት እናቴ ቤት ሄድኩ ። እናቴ ከአለሙ ጋር ተጣልቼ እንደሆነ አወቀች ።
እንደእናት ብዙ መከረችኝ: እንደጎደኛም አደመጠቺኝ ። "እኔ የብርሃነ ልጅ ነኝ ልክስክስነትን አልታገስም" አልኳት ።
"ያደግኩት አንቺን እና ብርሃነን እያየሁ ነው" አልኳት ። "ያደግኩት ሚስቱን እንደንግስት ከሚቆጥራት አባት ጋር ነው። ያደኩት ባሏን እንደንጉስ ከምታከብረው እናት ጋር ነው" አልኳት ።
ሳወራ ...ስፎክር.... ስቅለሰለስ፣ ሆድ ሲብሰኝ ... በማዘን ቃል ሳታወጣ ነበር የምትሰማኝ ።
እናት አይደለች ባሸንፍ እንኳን "ደከመሽ አይደል፣ ባተልሽ አይደል?" ብላ ደስታዋ ውስጥ ሳይቀር ማዘን ይኖረዋል!!
በሰባተኛው ቀን እንደዋዛ ... "ኤልሱ የኔ ኤልሳ" አለች
"አቤት ማሚ "
" ብርሃነ ከተጋባን በኋላ ከሌላ የወለደው ልጅ ነበረው ፤ ገመና ሆኖ የቀረው የወለደው ልጅ በለጋ እድሜው ስለተቀጠፈ እና ስለማይጠቅም ብለን ነው በፊትሽ አውርተን የማናውቀው " ብላ በሃዘኔታ አየችኝ ።
የሆነ ነገር ሲናድብኝ ፣ የሆነ ፍርሃት ሲያላውሰኝ እየታወቀኝ ነው ። የምናውቀው በሚመስለን
ጎጆ ውስጥ እንኳን ብዙ የማናውቀው እውነት ተቀብሯል ።
© Adhanom Mitiku
📱ከወደዱት ለወዳጅዎ ያጋሩት!📱
@bewketuseyoum19
@bewketuseyoum19Показать полностью ...