💥💞
#አልተዘዋወረችም💥💞
✍ አሌክስ አብርሃም
ክፍል ሃያ ሁለት
ፎቶ ኮፒ!
ቀጥሎ ምንድን ነው የሚሆነው? መሬታችንን እየሸረፍን ሸጠን አጨብጭበን ከመቅረታችን በፊት ምን ላድርግ? ነበር የዬቀኑ ሐሳቤ፡፡ ንግድ አሰብኩ፣ ግን እርግጠኛ ባልሆንኩበት ነገር ያቺን የመሬት ብር ደፍሬ መንካት አስፈራኝ፡፡ ከቤት ኪራይ የምናገኜው ገቢ ያን ያኽል የሚያወላዳ አልነበረም።እንዲያውም ከትምህርት ቤት ክፍያና ከታክሲ የሚያልፍም አልነበረም፡፡ ምናልባት አጋንኜው ይሆናል ግን ወደ ችግር እየተንደረደርን እንደነበር ነው በወቅቱ ይታዬኝ የነበረው። እማማን ላማክራት ስሞክር “አትጨነቅ መድኃኒዓለም ያውቃል'' ከማለት ያለፈ ምንም ነገር
ከአፏ አይወጣም ነበር፡፡ የእሷን ያኽል አማኝ ስላልሆንኩ ይሁን ወይም የአባቴ ሱቅ በግፍ ሲወሰድ መድኃኒዓለም ዝም ስላለ፣ ብቻ አባባሏ የባሰ ያስጨንቀኝ ነበር እንጂ ተስፋ አልሰጠኝም፡፡ እንዲሁ በጭንቀት ሌላ ሁለት ዓመታት ነጎዱ፡፡ ንግድ ሥራ ኮሌጅ በዋናው በር በኩል መንገዱን ተሻግሮ ሁለት ወጣት ወንድማማቾች የከፈቷት ፎቶ ኮፒ ቤት ነበረች፡፡ የኮሌጁ ተማሪ “ሃንድአውት" ኮፒ የሚያደርግባት፡፡ እውነቱን ለመናገር ወጣትና መልከመልካሞቹ ወንድማማቾችም ተጨዋችነታቼው ጋር ተዳምሮ ብዙውን ተማሪ የሚስብ አንዳች ነገር ነበራቸው፡፡ ከሁለት ዓመታት በላይ ደንበኞች ስለነበርን እንግባባለን፤ እንዲያውም ቅርርባችን የጓደኝነት ቅርጽ ይዞ ነበር፡፡ ለመድኃኒዓለም ዝክር ጠርቻቼው እቤታችን ከመጡ በኋላ ደግሞ እማማ የምትጠምቀው ጠላ ጋር በፍቅር ወድቀው ነበር፡፡ እሷም በተጠመቀ ቁጥር “ለነዚያ ልጆች ውሰድላቼው' ትላለች፡፡ በአምስት ሊትር ጀሪካን እወስድና ክላስ ስጨርስ እዚያች ቤት ተቀምጠን ጠላችንን እያንቃረርን የሞቀ የወጣትነት ወሪያችንን እናደራ ነበር፡፡ አንዳንዴ ተማሪ ሲበዛ የፎቶ ኮፒ ሥራቼውን አግዛቼው ስለነበር ቤተኛ ነበርኩ፡፡ የሆነ ቀን የሦስተኛ ዓመት ትምህርት እንደጀመርኩ አካባቢ ታናሽዬው ድንገት ከዚያች ሱቅ ጠፋ፤ የት ሄደ አልኩት? ታላቁን፤ ፊቱ ላይ ሐዘን እንዳጠላበት “የለም ባክህ” አለኝ፡፡ በሆነ ነገር ተጣልተው ይሆናል ብዬ ችላ አልኩት፡፡ ታናሸዬው ሞገደኛ ነገር ነበር፤ ይሁንና በተከታታይ ለሳምንት አካባቢ ጠፋ፡፡ ይኼ ሲገርመኝ ታላቅዬው እንድታግዘኝ ብሎ እዚያች ፎቶ ኮፒ ሱቅ ውስጥ አንዲት ልጅ ቀጠረ፤ የዚያን ጊዜ ግን ጠበቅ አድርጌ ጠየቅሁት “አሮን የት ሄደ?'' አሮን ነበር ስሙ። ልክ የተሳሳተ ነገር የጠየኩ ይመስል ኮስተር ብሎ “ና ቡና እንጠጣ” አለና እያጣደፈ ይዞኝ ወጥቶ ቴሌ ባር ወሰደኝ፡፡ ግራ ቀኝ ተገላምጦ ሰው አለመኖሩን ካረጋገጠ በኋላ ድምፁን ቀንሶ “ከአገር ወጣ” አለኝ፡፡ "ήλης Φ?" “አዎ! እንግሊዝ'' አለና እንደገና ዙሪያውን ቃኜት አደረገ፤ ምን ግራ ቀኝ አገላመጠው ብዬ መጀመሪያ ገርሞኝ ነበር፡፡ በኋላ ቀስ በቀስ አኪያሄዱን ሲነግረኝ ነገሩ ሕገወጥ
እንደሆነ ገባኝ፡፡ ይሁንና ልክ እንደመገለጥ የሆነ አዲስ ተስፋ አጫረብኝ። ለካ መሄድም አለ የሚል፣ ለካስ ዓለም ሰፊ ናት፣ ከኩሪያችን መውጣትም ይቻላል የሚል... እዚህ እጅ በእጅ ከመፋለም ራቅ ብሎ በዶላር ሚሳኤል ድሀነትን በጅምላ ማደባዬት ይቻላል የሚል ተስፋ። ከዚያን ቀን ጀምሮ ከአጀማመሩ እስከመዳረሻው ወሪያችን ይኼው ስደት ሆነ፡፡ አልፎ አልፎ ስለቤተሰቦቻችንም ጉዳይ አወራን። በተለይ እኔ በጥያቄ መቆሚያ መቀመጫ ስላሳጣሁት እስኪሰላች ወሬውን ከረምንበት። እኔም ፈጽሞ በአእምሮዬ የሌለ ነገር እንደ መንፈስ ገብቶብኝ፣ ቆሜም ተኝቼም ሐሳቤ ወደውጭ መሄድ ሆነ። ከብዙ ብዙ ወሬና ማጣራት በኋላ ይኼው ልጅ አንዲት መንግሥት ቢሮ ውስጥ የምትሠራ፣ ዕድሜዋ አምሳውን የተሻገረ ዘናጭ ሴት ጋር አስተዋወቀኝ (ማወቅ እንኳን አላውቃትም አገናኜኝ ማለቱ ይቀላል) በሷ በኩል ነበር፣ ከአዲስ አበባ እስከ እውሮፓ፣ ከዚያም አሜሪካ ድረስ በተዘረጋ ሕገወጥ ሰው አዘዋዋሪዎች ጉዞው የሚፈጸመው። ሴትዮዋ የመጣችው በወቅቱ ዘመናዊ በነበረ ቀይ 'ቶዮታ ላንድ ክሩዘር' መኪና ሲሆን፤መኪናውን የሚነዳው ወጣት ልጅ አንድም ነገር የማይናገር ግኡዝ ነገር ነበር፤ ልጁ ምንም የተለዬ እንቅስቃሴም ንግግርም ስላልነበረው መኪናው በራሱ የሚሄድ ነበር የሚመስለው። ከዋቢሸበሌ ሆቴል በር ላይ አሳፍረውን ወደ ፒያሳ እየተጓዝን፣ እዚያው መኪናው ላይ ስለሁኔታው በዝርዝር አስረዳችኝ። አነጋገሯ አጠር አጠር ያለና ግልጽ ነበር። ዝርዝሩ ሁለት አማራጮች ነበሩት ፈጠን ባለ ንግግር እንዲህ ስትል አብራራችልኝ "ጉዞው ከመነሻው እስከ መድረሻው ሕገወጥ ነው፤ ለጓደኛም ይሁን ለቤተሰብ ዝርዝር ጉዳዮችን ባትናገር ጥሩ ነው፤ በመንገድ ላይ ተይዞ መመለስም ሊኖር ይችላል፡፡ የተያዝከው በእኛ ስሕተት ከሆነ ገንዘብሀን ሙሉውን እንመልሳለን፤ ለመጓጓዣም ሆነ ለምግብ የምታወጣውን እንከፍላለን፤ ያ ብቻ ሳይሆን እንደገና አመቻችተን ጉዞሀን እንድትቀጥል እናደርጋለን፡፡ እስከ አሁን አንድም ሰው ተይዞ የተመለሰብን የለም። እንዲሁ እንድታውቀው ነው፤ ስሕተቱ የእንተ ከሆነ ግን
ገንዘብ በንመልስም ማስተካከል የሚቻል ስሕተት ከሆነ እንደገና ለመርዳት እንሞክራለን፤ ያም ሆኖ ግን ግዴታ አይኖርብንም!” የአንተ ስሕተት ማለት፣ ሰዓት አለማክበር፣ በቀጠሮው ቦታ አለመገኘት፣ እንድታርፍበት ከሚነገርሀ ቦታ ውጭ ወጥቶ በፖሊስ መያዝ፣ ሌሎች ሰዎች ጋር መጠላት፣ ክፍያን በአግባቡ አለመክፈል፣ በተለይ ክፍያና ሰዓት፣ አለችና “በተረፈ እምነትህን እኛ ላይ ጣለው። የቤተሰቦችህን አድራሽ ትነግረናለህ የደረስክበትን በየጊዜው እናሳውቃቼዋለን...ጉዞው ምን ያኽል ጊዜ እንደሚወስድ በትክክል ማወቅ አይቻልም። መንገድ ላይ በየአገራቱ እንደሚኖረው ሁኔታ ይወሰናል፡፡ ዋናው ነገር የትኛውም አገር ምንም ይፈጠር ከጎንህ ነን'' ካለች በኋላ “ታዲያ አሜሪካ ስትገባ እንዳትረሳኝ...ሽቶ እወዳለሁ እንድትልክልኝ" ብላ ፈገግ አለች፡፡ ይኼ የመጨረሻ ንግግሯ አሜሪካ እንደተነሳሁ የምደርስባት ቅርብ፣ ሀዋሳ፣ ቢሾፍቱ ነገር እንድትመስለኝ አድርጎኝ ነበር በወቅቱ፡፡ መልሰው ዋቢሸበሌ በር ላይ አውርደውን እንደገና ወደ ፒያሳ አቅጣጫ ተፈተለኩ። ያቺን ሴት ስሟን እንኳን አላውቀዉም፤ ሴትዮዋ ነበር የምንላት። ከዚያ የመኪና ውስጥ ማብራሪያ በኋላ ስደት መረጥኩ፡፡ ልቤ ቀድሞ ተነስቶ ነበርና ውሳኔዬ የዚያን ቀን ውጤት ብቻ ነው ማለት አልችልም። የወጣትነት ችኩል ስሜትም ይሁን፣ አልያም ተስፋ ያደረግሁት ነገር፣ ብቻ እነዚሀን ወደ ውጭ አገር እንወስድሃለን ያሉ ሰዎች አምኛቼው ነበር፡፡አሜሪካ ደግሞ የተስፋዬ ምድር ነበረች። ይኽ ዉሳኔ ለእኔ ቀላል አልነበረም፤ በተለይ እናቴንና ሁለት እህቶቼን ትቼ መሄድ ሙዳ ሥጋ ከሰውነቴ ላይ የመቦጨቅ ያኽል ነበር ሕመሙ። ከሸጥነው መሬት ላይ የተወሰነ ብር አንስቼ በድፍረት እግሬን ሳነሳ፣ የዩኒቨርስቲ ትምህርቴን ላጠናቅቅ አንድ ዓመት ብቻ ቀርቶኝ ነበር፤ ቢያንስ ጨርሰውና ሒድ እያሉኝ ጣጥዬው መንገዴን ጀመርኩ፡፡ የእናቴ የመጨረሻ ቃል ዕንባ በሚያደናቅፈው ድምፅ “መድኃኒያለም ከፊትህ ይቅደም!'' የሚል ነበር፡፡ ያኔ በቼልታ አሜን ብዬ ርምጃዬን አፈጠንኩ። ከዚያ በኋላ ግን ባለፍኩበት መንገድ ሁሉ ምርቃቷ ትዝ ሲለኝ፣ በሙሉ
ልቤ፣ ከነፍሴ በወጣ ስሜት አሜን፤ ያላልኩበት ጊዜ የለም፡፡ መቼስ ምርቃት እንደ ምግብና ቁሳቁስ መጠቀሚያ ጊዜው አያልፍ! ስደትን እንዲሀ ከፎቶ ኮፒ ቤት ኮፒ አደረግኋት።
እኔን! እየተባልን አድገን...Show more ...